Friday, June 12, 2015

ክፍል አምስት ንዑስ ክፍል ሦስት ብዙ ዓይነትና ተለዋዋጭ የሆኑ ጥቅሶችን በአንድ ባለቤት ባለው ነገር ውስጥ ማነጻጸር Comparing Various Verses on the same Subject

ክፍል አምስት


ንዑስ ክፍል ሦስት


ብዙ ዓይነትና ተለዋዋጭ የሆኑ ጥቅሶችን በአንድ ባለቤት ባለው ነገር ውስጥ ማነጻጸር


Comparing Various Verses  on the same Subject  


የተወደዳችሁ ወገኖች በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 3 ቊጥር 16 መሠረት የዘላለምን ሕይወት መፈለግ አስመልክቶ በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 19 ቊጥር 16 እና 17 ላይ የተጠቀሰለትን  አንድ ወጣት ሰው አንስተን የዘላለምን ሕይወት እንዳገኝ ምን መልካም ነገር ላድርግ ? አለው እርሱም፦ ስለ መልካም ነገር ለምን ትጠይቀኛለህ ? መልካም የሆነ አንድ ነው፤ ወደ ሕይወት መግባት ብትወድ ግን ትእዛዛትን ጠብቅ አለው የሚለውን የጌታችንን መልስ ተመልክተን ነበር ታድያ ከዚሁ ሃሳብ ጋር አያይዘን ያየነው ሃሳብ ነበር እርሱም እስከዛሬ ድረስ ያለው የብዙ ሰው ጥያቄ የዚህ የወጣቱ ጥያቄ አለመሆኑንና ከዚህ ይልቅ በዚህ ምድር ሳለ ያላሟላውን ሊሟላለት የሚፈልገውን ነገር ብቻ ነው ማንሳት የሚፈልገው ብለን  መጽሐፍቅዱሳችን የሰው ሕይወት በገንዘቡ ብዛት አይደለምና ተጠንቀቁ፥ ከመጐምጀትም ሁሉ ተጠበቁ በማለት የአንድን ባለጠጋ ሰው ታሪክ ከሉቃስ ወንጌል 12 16 _ 31 በማንሳትና ከሌሎችም ጥቅሶች ጋር በማያያዝ እግዚአብሔር በዚህ በምድር ባለ ነገር ሁሉ ማግኘታችንን እና መበልጸጋችንን ባይጠላም የእግዚአብሔርን መንግሥት ግን የሕይወታችን ተቀዳሚ ልናደርግ መንግሥቱንም በቅድሚያ ልንፈልግ እንደሚገባ አያይዘንም በዚህ ምድር ያለ ባለጸግነት የሚያልፍ መሆኑንና ተስፋ ልናደርገው የማይገባ መሆኑንም 1 ጢሞቴዎስ 6 17 _ 19 የተጠቀሰውን ሃሳብ አንስተን በሰፊው ተማምረናል ዛሬም ከዚሁ የቀጠለውን ሃሳብ በስፋት እንመለከታለን የአምላኩን እውቀትና በተጨማሪም የገንዘቡን አያያዝ ምክር በማይፈልግ ዓለም ውስጥ ነው የምንኖረው ጥቂት ሰዎች ግን ሃብትን ማለትም ገንዘብን እንዴት ማጠራቀምና መሰብሰብ እንደሚገባ መጽሐፍቅዱስ የያዘውን አስደናቂ የሆነ እውቀት ይዘዋል እኛን ባለጸጎችና ደስተኞች ሊያደርገን እግዚአብሔር ይፈልጋል በ3ኛ ዮሐንስ ቊጥር 2 ላይ ወዳጅ ሆይ፥ ነፍስህ  እንደሚከናወን፥ በነገር ሁሉ እንዲከናወንልህና ጤና እንዲኖርህ እጸልያለሁ ይለናል በነገር ሁሉ መከናወን የሚመጣው ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው ነገር ግን እግዚአብሔር የነገረን መንፈሳዊ ዋጋ ከሥጋዊ ነገር በጣም እንደሚበልጥና እርሱን በቅድሚያ መፈለግ እንዳለብን ነው የእርሱ መንግሥት ከዚህ ዓለም ነገር የሚበልጥ ነውና ይህንን በምናደርግበት ጊዜ አስፈላጊያችን በሆነው በሚታየው ነገር አቅርቦት ሊያደርግልንና ሊሰጠን ቃል ገብቶልናል በማቴዎስ ወንጌል 6 19 _ 24 ላይ ብልና ዝገት በሚያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በሚሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በምድር ላይ መዝገብ አትሰብስቡ ነገር ግን ብልም ዝገትም በማያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በማይሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በሰማይ መዝገብ ሰብስቡ መዝገብህ ባለበት ልብህ ደግሞ በዚያ ይሆናልና ዓይንህ ግን ታማሚ ብትሆን፥ ሰውነ ትህ ሁሉ የጨለመ ይሆናል  እንግዲህ በአንተ ያለው ብርሃን ጨለማ ከሆነ፥ ጨለማውስ እንዴት ይበረታ፦ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ማንም የለም፤ ወይም አንዱን ይጠላል ሁለተኛውንም ይወዳል፤ ወይም ወደ አንዱ ይጠጋል ሁለተኛውንም ይንቃል፤ ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም በማለት ያዘናል እውነተኛውን ገንዘባችንን በተደላደለ እና በተጠበቀ ሁኔታ ለማስቀመጥ ለእግዚአብሔር እውቅና መስጠትና እግዚአብሔርን ተቀዳሚ ማድረግ በጣም አስፈላጊ ነው ከሁሉም በኋላ እርሱ ተቀዳሚ የበረከት ምንጫችን ይሆናል  መጽሐፍቅዱሳችን በ1ኛ ጢሞቴዎስ 6 10 ላይ ገንዘብን መውደድ የክፋት ሁሉ ሥር ነውና፥ አንዳንዶች ይህን ሲመኙ፥ ከሃይማኖት ተሳስተው በብዙ ሥቃይ ራሳቸውን ወጉ ይለናል በዘጸአት 20 17 ላይ ደግሞ የባልንጀራህን ቤት አትመኝ የባልንጀራህን ሚስት ሎሌውንም ገረዱንም በሬውንም አህያውንም ከባልንጀራህ ገንዘብ ሁሉ ማናቸውንም አትመኝ ይለናል ነቢዩ ኤርምያስ የይሁዳን ንጉሥ በእርሱ የዜግነት ሀገር ውስጥ የሰውን ንብረት መከጀልና መቀማት እንደማይገባው ሲገልጽለት  ደግሞ ዓይንህና ልብህ ግን ለስስት  ንጹሕ ደምንም ለማፍሰስ ዓመፅንና ግፍንም ለመሥራት ብቻ ነው አለው ትንቢተ ኤርምያስ 22 17 እንደገናም ይህንኑ  ገንዘብን በተመለከተም ጌታችን ኢየሱስም በሉቃስ ወንጌል 12 15 _ 34 መሠረት የሰው ሕይወት በገንዘቡ ብዛት አይደለምና ተጠንቀቁ፥ ከመጐምጀትም ሁሉ ተጠበቁ…………….. ሲል  ሃይለኛ ማስጠንቀቅያ ሰጥቶአል ከዚህ የተነሳ ነው እንግዲህ የዕብራውያን ጸሐፊ አካሄዳችሁ ገንዘብን ያለ መውደድ ይሁን፥ ያላችሁም ይብቃችሁ፤ እርሱ ራሱ አልለቅ ህም ከቶም አልተውህም ብሎአልና ሲል የጻፈልን የሀገራችን ሰዎች አተርፍ ባይ አጉዳይ እንዲሉ  ብዙ ሰዎች እንግዲህ በራሳቸው ጽኑ ምኞትና ፍላጎት በሀብት ላይ ሀብት እናገኛለን ሲሉ የከባድ መከራና ስቃይ ምርኮኞች ይሆናሉ ለዚህም ምርኮኞች ለሆኑበት ነገር  ሳይወዱ ግድ ይሆንባቸውና እውቅናን ይሰጣሉ ጌታ እግዚአብሔር ከዚህ ይጠብቀን የምናነበውንም ቃል ባርኮ በዚህ ነገር የሳትንና የተሳሳትን ሌሎችንም ያሳሳትን ብንኖር ወደ እውነቱ ይመልሰን አሜን


ቀሲስ ዮናስ ጌታነህ








No comments:

Post a Comment