Wednesday, November 25, 2015

M2U00056 መዝገብነ ዘኢይረክቦ ሠራቂ ሌባ የማያገኘው መዝገባችን ክፍል ሦስት መዝገብነ ዘኢይረክቦ ሰራቂ ወኢያማስኖ ፃፄ ወቊንቊኔ ውእቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ትርጉም ፦ ሌባ የማያገኘው ብል ነቀዝ የማያበላሸው መዝገባችን ይህ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ( ምንጭ መጽሐፈ ሰዓታት ) በክፍል ሦስት ትምህርታችን መዝገብን የምንመለከትበት ሌላው የእግዚአብሔር ቃል መንገድ አለ እርሱም ምንድነው ስንል መዝገብ የሰው ልጆችን መላ ማንነት እና ሕይወትን የመስጠት ፣ አስተሳሰብን ፣ ስሜትን ፣ አትኩሮ ማሰብን ፣ ጥንቃቄን ፣ ዓላማንና ግብን ሳይቀር የሚጠይቅ ጉዳይ ነው ሰዎች እግዚአብሔርን ሲያመልኩት ፣ ሲወዱት በጥብቅ ፍላጎት ነው ለዚያ ነገር ጠንካራ ስሜት አላቸው ማለትም በእንግሊዘኛው Passionate ናቸው ማለትም ጊዜያቸውን ፣ ኃይላቸውን ፍላጎታቸውን ለመደሰት ብቻ ሲሉ የሚሰሩትን ሥራ ሁሉ የሚያውሉት ለዚሁ ነገር ነው ታድያ ይህ ሁሉ የሰዎች ማንነትና መላ ሕይወት የተሰጠበት ነገር ነው መዝገብ የሚባለው ለዚህም ነው እነዚህን ሁሉ የዘረዘርኳቸውን እውነቶች መጽሐፍቅዱሳችን ሊያሳየን ፈልጎ ብልና ዝገት በሚያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በሚሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በምድር ላይ መዝገብ አትሰብስቡ፤ ነገር ግን ብልም ዝገትም በማያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በማይሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በሰማይ መዝገብ ሰብስቡ ፤ መዝገብህ ባለበት ልብህ ደግሞ በዚያ ይሆናልና ያለን የማቴዎስ ወንጌል 6 ፥ 19 _ 21 በዚህ ምድር ላለ ጥቅም ፣ ይሰጠናል ብለን ለምናስበው ለማንኛውም ነገር ትኩረት መስጠት አስፈላጊና በጣምም ጠቃሚ ነገር ነው ብለን እናምናለን በምድር እስካለን ድረስ ጠቃሚያችን ነውና ይህን ማድረጉ መልካም ነው ተገቢም ነገር ነው ነገር ግን ሁኔታውን ከእግዚአብሔር በላይ አግዝፈንና ቆጥረን ከእግዚአብሔርም ይልቅ ፊተኛ አድርገን በዛ ነገር ብቻ ተይዘን ብንቀር ያ ይጠቅመናል ብለን ጊዜያችንን ኃይላችንን ፍላጎታችንንና የመሣሠሉትን ሁሉ የሰጠንበት ነገር ድንገት ሳናስበው ከእጃችን ሊወጣ ይችላል እንደገናም ብል ዝገት ሊያገኘው ሌቦችም ቆፍረው ሊሰርቁት ይችላሉ በመሆኑም ያንን ሊጠቁመን ፈልጎ ወንጌላዊው ማቴዎስ ብልና ዝገት በሚያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በሚሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በምድር ላይ መዝገብ አትሰብስቡ አለን ስለዚህ አሁንም መሰብሰብ መልካም አይደለም ባንልም ስንሰበስብ ግን ተስፋችንን በምድር ላይ ብቻ በማድረግ እንግዲህ ነፍሴ ሆይ ብዪ ጠጪ ጥገቢ ደስም ይበልሽ ስንል ልንሰበስብ አይገባም እንደገናም ከጌታ ጋር ሆነን እንጂ ለብቻችን ሆነን መሰብሰብም የለብንም ምክንያቱም መጽሐፍ ሲናገር ከእኔ ጋር ያልሆነ ይቃወመኛል፥ ከእኔ ጋርም የማያከማች ይበትናል ይለናልና የማቴዎስ ወንጌል 12 ፥ 30 ፤ የሉቃስ ወንጌል 11 ፥ 23 ከዚህም ሌላ በሉቃስ ወንጌል 12 ፥ 13 _ 31 የተጻፈልንን የምንባብ ክፍል እንመልከት አያይዞም ወንጌላዊው ማቴዎስ ለእናንተ ብልም ዝገትም በማያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በማይሠርቁት ዘንድ በሰማይ መዝገብ ሰብስቡ ፤ መዝገብህ ባለበት ልብህ ደግሞ በዚያ ይሆናልና አለን የማቴዎስ ወንጌል 6 ፥ 19 _ 21 ታድያ ብልም ዝገትም የማያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው የማይሠርቁት እኛም ሰብስቡ የተባልነው አንደኛውና ዋነኛው የሰማይ መዝገብ የመጽሐፈ ሰዓታት ደራሲ እንደነገረን በግዕዙ ቃል መዝገብነ ዘኢይረክቦ ሰራቂ ወኢያማስኖ ፃፄ ወቊንቊኔ ውእቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ይለናልና ሌባ የማያገኘው ብል ነቀዝ የማያበላሸው ለእናንተ በሰማይ መዝገብ ሰብስቡ የተባልነው መዝገባችን ይህ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ይህ መዝገባችን ኢየሱስ ደግም ሰብስበን ያገኘነው መዝገብ ሳይሆን እንድንበት ዘንድ እግዚአብሔር አብ በነጻ የሰጠን ታላቅ የመዳናችን መዝገብ ነው የሐዋርያት ሥራ 4 ፥ 12 የእግዚአብሔር ልጅ የናዝሬቱ ኢየሱስ ስለበደላችን ሞቶ እኛን ስለማጽደቅ ከሞት ሲነሳ በተራ ሰውነት አይቶ እዚያው በመቃብር ውስጥ ሊያስቀረው የምድር የሆነው ብል ነቀዝ አልበላውም የካህናት አለቆች ጸሐፍት ፈሪሳውያን ከጲላጦስ ጋር በመመሳጠር ሌባ ሰረቀው ሲሉ ሊያስወሩ እንደወደዱት እና እንዳስወሩትም ሁሉ ሌባም አልሰረቀውም እርሱ እንደተናገረው የተለየ መዝገባችን ሊሆን በሦስተኛው ቀን የተነሣ ነውና መቃብሩ ባዶ ነው የማቴዎስ ወንጌል 27 ፥ 62 _ 66 ፤ የማቴዎስ ወንጌል 28 ፥ 1 _ 15 ድንጋዩና መቃብሩ ጠባቂዎችም ሳይቀሩ ያልቻሉትን ጌታ ሌባውም ሆነ ብል ነቀዙ የሚሰርቀውና የሚበላው አይደለም ለዚህም ነው መላኩ ለሴቶቹ እናንተስ አትፍሩ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንድትሹ አውቃለሁና እንደተናገረ ተነስቶአልና በዚህ የለም የተኛበትን ሥፍራ ኑና እዩ ሲል የተናገረው የማቴዎስ ወንጌል 28 ፥ 5 ታድያ ይህንን ጌታ ሌባ ያገኘውና ብል ነቀዝም ያበላሸው ቢሆን ኖሮ መልአኩ ይህንን መለኮታዊ እውነታ ሊናገር ይደፍራልን ? የመጽሐፈ ሰዓታት ደራሲስ ሌባ የማያገኘው ብል ነቀዝ የማያበላሸው መዝገባችን ይህ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ይለው ነበርን ? በመሆኑም በዚህ ጉዳይ ላይ መልሱን ለእናንተ ለወገኖቼ ብተወዉ እንኳ አይለውም እንደምትሉኝ በጣም እርግጠኛ ነኝ ለምን ብትሉኝ ሌባ የማያገኘው ብል ነቀዝ የማያበላሸው መዝገባችን ይህ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ያለው የመጽሐፈ ሰዓታት ደራሲ ብቻ ሳይሆን ወንጌሉም ሳይቀር ነገር ግን ብልም ዝገትም በማያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በማይሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በሰማይ መዝገብ ሰብስቡ ስላለን ብልም ሆነ ዝገት ያላጠፋው ሌቦችም ቆፍረው ያልሠረቁት እውነተኛውና ዋነኛው የሰማይ መዝገባችን ኢየሱስ ክርስቶስ እና በኢየሱስ ክርስቶስም በኩል የምናገኘው ሽልማታችን ነው የመጽሐፈ ሰዓታት ደራሲ ሐመርነ ዘኢይቀርቦ ሞገድ እንዳለው ሁሉ አሁን እዚህ ጋር ደግሞ መዝገብነ ዘኢይረክቦ ሠራቂ ብሎታል ወደ አማርኛው ስተረጉመው የዚሁ የመጽሐፈ ሰዓታቱ ደራሲ ኢየሱስን ማዕበል የማይቀርበው መርከባችን እንዳለው ሁሉ ሌባ የማያገኘው መዝገባችንም ብሎታል በመሆኑም ይህ የእግዚአብሔር ልጅ የናዝሬቱ ጌታ ከማዕበሉ የታደገን ብቸኛው መርከባችንና ከሌባውም ሆነ ከብል ነቀዙ ያስመለጠን ብቸኛው መዝገባችን ነው ክብር ከዘላለም እስከ ዘላለም ለእርሱ ለታረደው በግ ለጌታችን ለኢየሱስ ክብር ይሁንለት የተሰቀለው ኢየሱስ ሲነሳ ለብቻውና ለራሱም ብቻ ብሎ የተነሳ ጌታ ሳይሆን ላንቀላፉት ሁሉ በኲራት ሆኖ ከሙታንም ተለይቶ የተነሣ ጌታ በመሆኑ እርሱን ያላገኘው ፣ ላግኝ ቢልም ማግኘት የማይችለው ሌባው ብሉና ነቀዙ እኛንም አያገኘንም ኢየሱስን እንግዲህ መዝገባችን ያሰኘው ይሄ ጉዳይ ነው ሌባውና ነቀዙ ሳያገኘውና ሳይሠርቀው የመቃብሩ ድንጋይም ሳያስቀረው ሞትን አሸንፎ በድል የተነሣ ወደ አባቱም ቀኝ አርጎ በክብር በመቀመጥ ለእኛ የሚማልድልን እንደገናም በዓለም ፍጻሜ ሊወስደን ተመልሶ የሚመጣልን በመሆኑ እውነተኛው መዝገባችን ነው ስለዚህ አሁንም ወንጌላዊው ማቴዎስ እንደነገረን እኛም መዝገባችን ባለበት ልባችንም በዚያው ሊሆን ይገባል የተወደዳችሁ ወገኖች በክፍል አራት ትምህርታችን ላይ ደግሞ ሌባ የማይሠርቀው መዝገባችን የተባለበትን ሌላውንና ዋናውን ምክንያት ከመጽሐፍቅዱሳችን ጋር በማመሳከር የምንመለከተው ይሆናል ወገኖቼ ትምህርቱ እንዳያመልጣችሁ በየተራ የሚለቀቁትን ሁሉ ጊዜ ሰጥታችሁ እንድትመለከቱአቸው ይሁን ስል ለማሳሰብ እወዳለሁ የቃሉን ደጅ ከፍቶ ያስተማረን የእግዚአብሔር መንፈስ ለዘለዓለም የተባረከ ይሁን ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን Joshua Breakthrough Renewal Teaching and Preaching Ministry አገልጋይና ባለ ራዕይ ቀሲስ አባ ዮናስ ጌታነህ

No comments:

Post a Comment