Monday, March 9, 2015

ተሰቅለ በእንቲአነ ወበመስቀሉ ኮነ ሕይወትነ ጽንዕነ ቤዛነ ስለእኛ ተሰቀለ በመስቀሉም ጽናችን ቤዛችን ድኅነታችን ተደረገልን

ይህ Joshua Breakthrough Renewal Teaching and Preaching Ministry
ሥር የሚቀርብላችሁ ትምህርት ነው



ተሰቅለ በእንቲአነ ወበመስቀሉ ኮነ ሕይወትነ ጽንዕነ ቤዛነ


ስለእኛ ተሰቀለ በመስቀሉም ጽናችን ቤዛችን ድኅነታችን ተደረገልን


ሃይማኖተ አበው


እልመስጦአግያ


ምዕራፍ አራት


ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን
በእንጨት ላይ ተሸከመ በመገረፉ ቁስል ተፈወሳችሁ

1ኛ ጴጥሮስ 2 24


የተወደዳችሁ ወገኖች ዛሬ የምንመለከተው እነዚህን በሃይማኖተ አበው የተጻፈውንና ጴጥሮስ በመልዕክቱ የጠቀሰልንን ሃሳቦች በማገናኘት በማዛመድም ነው ሁለቱም ሃሳቦች ማለት በጴጥሮስ መልዕክት የተጠቀሰውና በሃይማኖተ አበው የተጻፉት ሃሳቦች አንድ ዓይነት ናቸው ሁለቱም ሃሳቦች በደኅንነታችንና በፈውሳችን ዙርያ እርግጠኞች ሆነን ክርስቶስ ለጽድቃችን ለመዳናችን ለመጽናታችንም በመስቀል ላይ በሞቱ የሠራውን ሥራ በእምነት እንድንቀበል የሚያስታውሱንና የሚናገሩን ናቸው ሃይማኖተ አበው የተባለው መጽሐፍ ስለእኛ ተሰቀለ በመስቀሉም ጽናችን ቤዛችን ድኅነታችን ተደረገልን ሲል በእግዚአብሔር ቃል ላይ በዚሁ በ1ኛ ጴጥሮስ 2 24 ላይ የተጠቀሰውን ሃሳብ  የመነሻ ሃሳብና  ተጠቃሽ ቃል አድርጎ በመውሰድ ነው ሊጠቁመን የፈለገው የእግዚአብሔርን ቃል የመነሻ ሃሳብ ወይንም  አስረጂ አድርጎ የተነሳ ማንኛውም ጽሑፍ መነሻ አድርጎ ከተነሳበት ሃሳብ ጋር ብቻ ሳይሆን ከጠቅላላው የመጽሐፍቅዱስ ሃሳብ ጋር ትክክል ከሆነ ጽሑፍ ትክክል ነው ማለት ነው ለዚህ ነው የሃይማኖተ አበውን ሃሳብ መነሻ አድርገን በመጥቀስ እና ከእግዚአብሔር ቃል ጋር በማመሳከር የአሁንዋ ሳይሆን የጥንትዋ ኦርቶዶክሳዊት ሐዋርያዊት ዓለማቀፋዊት እናት ቤተክርስቲያን አስተምህሮዋ መጽሐፍቅዱሳዊ ነውና የአሁንዋ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን መጽሐፍቅዱሳዊ አስተምሕሮ እንደ ጥንቷ ኦርቶዶክሳዊት ሐዋርያዊትና ዓለማቀፋዊት ቤተክርስቲያን መሠረተ እምነቷ በእግዚአብሔር ቃል ተስተካክሎ ወደ ጥንተ መሠረቷ ትመለስ አስተምሕሮዋንም ሆነ ማንነቷን በዚሁ በተገለጠው በእግዚአብሔር ቃል ታድስ የምንለው ድህንነታችን እና በኃጢአት ምክንያት የመጣብን የቁስለት መፈወስ በኢየሱስ ሞት ተረጋግጦአል ምክንያቱም ኢየሱስ ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ በማለት ጴጥሮስ ይነግረናል ስለዚህ ዛሬ ተገርፎና ቆስሎ ፈውስን ባመጣልን ኃጢአታችንንም በእንጨት ላይ በተሸከመልን በዚሁ ጌታ አምነን በመዳንና በመፈወስም በዚህ በሞተልን ጌታ ምክንያት ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር እንነሳሳለን እንጂ እንደገና ይሄ ጌታ ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ እንዳልተሸከመልን እንዳልተገረፈልንና እንዳልቆሰለልን ፈውስንም እንዳልሰጠን በመቁጠር መዳንን ለማግኘት ብለን እንደገናም ወደኋላ ተመልሰን ተራራ አንወጣም ቁልቁለትም አንወርድም ዋሻ ለዋሻ ሰንሰለት ታጥቀን አንቅበዘበዝም ሰሌን ላይ አንተኛም ድንጋይ አንንተራስም ከዚህ ሌላም ደግሞ ለመዳን ስንል አሻሮ አንቆላም ዝክር አናዘክርም ማነህ ባለሳምንት ማነሽ ባለሳምንት ያስጠምድህ ያስጠምድሽ በአስራስምንትና የመሳሰሉትን ልንባልም  ቆሎ ስንቆላ ጉዝጓዝ ስንጎዘጉዝ ማሰሮ ስናሟሽና ሱቲም ስናለብስ ጎንበስ ቀናም ስንል አንገኝም ጌታችን ኢየሱስ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ የተሸከመልንና በመገረፉም ቁስል የፈወሰን ስለሆነ ለኃጢአት ሞተን  ለጽድቅ የምንኖርበት ጊዜ እንጂ ይህን በቀራንዮ መስቀል ላይ ለደኅንነታችን ሲል ዕርቃኑን የሞተልንን መራራ ሐሞትንም የጠጣልንን በጦርም የተወጋልንን ጌታ አይተን እንዳላየን በመቁጠር እንድናለን ስንል እንደገና ወደኋላ ሄደን አሻሮ ልንቆላ ድግስ ልንደግስ እሽቁልቁሊት የምንሄድበትና የምንንከባለልበት ጊዜ አይደለም በዚያ መንገድ ላይ ዕልህ ገብቶን የወንጌሉንም እውነት አሻፈረኝ ስንል አልሰማ ብለን ቃሉ ያላሳየንን እሽቁልቁሊቱን መንገድ በመምረጥ በዚያ መንገድ ላይ ስንምዘገዘግ ብንውል ግን ትርፉ ከመንከባለል ሌላም ወድቆ መላላጥና መገጣጠብም ነው የሚሆንብን ከጴጥሮስ መልዕክትም ሌላ የሃይማኖተ አበውም መጽሐፍ እንደነገረን ኢየሱስ ስለ እኛ የተሰቀለ ስለሆነ በመስቀሉ ማለት በእርሱ በኩል ጽናችን ቤዛችን ድኅነታችን ተደረገልን ስለዚህ ኢየሱስ ስለእኛ የተሰቀለ በመሆኑ ከእርሱ ውጪ ጽንዕ ቤዛና ድኅነት ወይም ሕይወት ሊሆንልን የሚችል ማንም የለም ሊኖርም አይችልም የሃይማኖተ አበው ጸሐፊ ጽንዕ ሲል ጌታችን ኢየሱስ በጽኑዕ ያዳነን ነውና ጽንዓታችን መሆኑን ሊያሳየን ነው መጽሐፉም ሲነግረን ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል ይለናል ዕብራውያን 7 25 እንደገናም እንግዲህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ በመረቀልን በአዲስና በሕያው መንገድ ወደ ቅድስት በኢየሱስ ደም በመጋረጃው ማለት በሥጋው በኩል እንድንገባ ድፍረት ስላለን በእግዚአብሔርም ቤት ላይ የሆነ ታላቅ ካህን ስላለን ከክፉ ሕሊና ለመንጻት ልባችንን ተረጭተን ሰውነታችንንም በጥሩ ውኃ ታጥበን በተረዳንበት እምነት በቅን ልብ እንቅረብ ይለናል ዕብራውያን 10 19 _ 22 ስለዚህ ኢየሱስ በመረቀልን በአዲስና በሕያው መንገድ ወደ ቅድስት በራሱ ደም በመጋረጃው ማለት በሥጋው በኩል እንድንገባ ድፍረትን የሰጠን እንደገናም በሌላ ሳይሆን በእርሱ በኩል ወደ እግዚአብሔር የመጣን በመሆናችን ፈጽሞ ያዳነን ነውና ጽንአችን ማለትም ጽንአታችን ነው ከዚህ ውጪ ሌላ የመዳኛ አማራጭ መንገድ የለም ለዚህም ነው ጌታ ኢየሱስም እንግዲህ  አማን አማን እብለክሙ ዘኢቦአ እንተ አንቀጽ ውስተ ዐፀደ አባግዕ ወአርገ እንተ ካልእ ገጽ ሰራቂ ወጉሕልያ ውእቱ ወዘሰ እንተ አንቀጽ ይበውዕ ኖላዌ አባግዕ ውእቱ የሚለን ትርጉም እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ወደ በጎች በረት በበሩ የማይገባ በሌላ መንገድ ግን የሚወጣ እርሱ ሌባ ወንበዴም ነው በበሩ የሚገባ ግን የበጎች እረኛ ነው የዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 10 1 እና 2 እንመልከት በመሆኑም ኢየሱስ እውነተኛ የበጎች በር ስለሆነ ሳንፈራና ሳንጠራጠር አምነን በዚሁ በር እንግባ በዚህ በር ልንገባ ሳንፈልግ በሌላ በር ልንገባ ብንፈልግ ግን  በር ወይንም መስኮት ሰባሪ እንደሆነው ሌባና ወንበዴ እንሆናለን በዚህ በር ስንገባ ግን እንድናለን እንገባለን እንወጣለን መሰማርያም እናገኛለን የዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 10 የተወደዳችሁ ይህን መልዕክት የምታነቡ የእግዚአብሔር ሕዝቦች ሁሉ የምናነበው ቃል ለሕይወትና ለመዳን ይሁንልን እግዚአብሔር ሁላችንንም ይባርክ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን



ቀሲስ አባ ዮናስ ጌታነህ

No comments:

Post a Comment