Friday, March 13, 2015

የሰዎች የእድገት መለኪያ አገልግሎትና የአገልግሎት ስም ማግኘት በሃላፊነት ቦታ ተቀምጦ ቤተክርስቲያንን ማስተዳደር መምራት መስበክ መዘመር ማሸብሸብ መዝለል እልል ማለትና የመሳሰሉት አይደሉም

ቤተክርስቲያን


ክፍል ስምንት


የሰዎች የእድገት መለኪያ አገልግሎትና የአገልግሎት ስም ማግኘት በሃላፊነት ቦታ ተቀምጦ ቤተክርስቲያንን ማስተዳደር መምራት መስበክ መዘመር ማሸብሸብ መዝለል እልል ማለትና የመሳሰሉት አይደሉም እነዚህ ሁሉ አስፈላጊያችን ሆነው እንደተጠበቁ ቢሆኑም ወደ ክርስቶስ መልክ ካላደረሱን ዋጋ የለውም ትልቁ ግባችን ማገልገላችንም ሆነ መገልገላችን የክርስቶስን መልክ ልንመስል ነው የክርስቶስን መልክ ልንመስል ተጠርተናልና ወደ ክርስቶስ መልክ ለመድረስ ነው ይህን ያልኩበት ምክንያት በክፍል አራት አራት ካነሳሁት ሃሳብ ጋር የዛሬውን የክፍል ስምንት ትምህርቴን ላያይዝ ፈልጌ ነው በክፍል አራት ትምህርት ላይ እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ ስላለን ቃሉ የዓለም ብርሃን ለመሆንና እንደ ብርሃን ልጆች ለመመላለስም በፊልጵስዩስ 2 14 _ 16 የተጻፈልንን ቃል በመጥቀስ ዛሬ የሕይወትን ቃል ብናቀርብም ቃላችንና ሕይወታችን የተለያየ በመሆኑ የፊልጵስዩስ መጽሐፍ ከተናገረው ቃል በተቃራኒው ነን የዋሆች አይደለንም ነውር ያለብን የእግዚአብሔር ልጆች ማለት ጠማሞችና ወልገድጋዶች ነን ክፉም ሳታስቡ ብንባልም አንጎራጋሪዎችና ክፉዎች ነን ሁሉን አድርጉ ተብለን ሳለ ሁሉን አናደርግም ለእኛ የሚጠቅመንን ያዋጣናል ሊያስኬደን ይችላል ብለን ከምናስበው ነገር ውጪ የምናደርገው ነገር እንደሌለ ይህ ደግሞ መልካም አለመሆኑን እና እግዚአብሔርም የማይደሰትበት ለሰዎችም ሳይቀር እንቅፋት እየሆነ የመጣ ነገር መሆኑን በሰፊው ተማምረናል በዚህ በክፍል ስምንት አበክረን የምንመለከተው በአገልግሎት ተጠምደን የሕይወትን ቃል የምናቀርብ ቢሆንም ሕይወታችንና ኑሮአችን ግን አንድ ዓይነት ባለመሆኑ የዋሆች አይደለንም ነውር ያለብን የእግዚአብሔር ልጆች ነን እናንጎራጉራለን ክፉ እናስባለን ወዘተርፈ ታድያ ከዚህ ሕይወት  እንዴት ነው መውጣት የምንችለው ? ይህንንስ አስበነው እናውቃለን ወይ ? የሚለውን መጠይቅ ለአገልጋዮች ለመሪዎች ለቅዱሳን ምዕመናንና ለሁሉም ሰው የማቀርበው ጥያቄ ነው በዓለም እንደብርሃን ልጆች የሚያሳየን መድረኩን ያጣበበው አገልግሎታችን ስብከታችንና ዝማሬዎቻችን አይደሉም እውነተኛው ክርስቶስን ሊመስል የተለወጠውና እየተለወጠ ያለው ሕይወታችን ነው ነገር ግን ከዚህ በተቃራኒው በዓለም እንደብርሃን ልጆች የሚያሳየን ስብከታችን ዝማሬያችን ስማችን በሃላፊነት ቦታ መቀመጣችን መምራት ማስተዳደራችን እየመሰለን ቅንነትንና የዋህነትን አጥተን አጠገባችን ካሉት ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ጋር በትንሽ በትልቁ ስንነቋቆር ስንተማማና ስንነካከስ እርስ በእርስ በአገልግሎትና በመድረክ ስጠኝ አትሥጠኝ ወይም ሰጠኸኝ አልሰጠኸኝ ስንዋቀስ ስንካሰስና ስንደባደብ እንታያለን ታድያ በዚህ ውስጥ ስላለን ማንን እንደምናገለግልና የምናገለግለውንም ጌታ እንኳ በትክክል ያላወቅን መሆናችን በጉልህ ይታያል ለዚህ ነው በኢሳይያስ መጽሐፍ ላይ የመሥዋዕታችሁ ብዛት ለእኔ ምን ይጠቅመኛል ?  ይላል እግዚአብሔር የሚቃጠለውን የአውራ በግ መሥዋዕትንና የፍሪዳን ስብ ጠግቤያለሁ የበሬና የበግ ጠቦት የአውራ ፍየልም ደም ደስ አያሰኘኝም  በእኔ ፊት ልትታዩ ብትመጡ ይህን የመቅደሴን አደባባይ መርገጣችሁን ከእጃችሁ የሚሻ ማን ነው ? ምናምንቴውን ቍርባን ጨምራችሁ አታምጡ ዕጣን በእኔ ዘንድ አጸያፊ ነው መባቻችሁንና ሰንበታችሁን በጉባኤ መሰብሰባችሁን አልወዽም በደልንም የተቀደሰውንም ጉባኤ አልታገሥም መባቻችሁንና በዓላቶቻችሁን ነፍሴ ጠልታለች ሸክም ሆነውብኛል፥ ልታገሣቸውም ደክሜያለሁ እጃችሁንም ወደ እኔ ብትዘረጉ ዓይኔን ከእናንተ እሰውራለሁ፥ ልመናንም ብታበዙ አልሰማችሁም እጆቻችሁ ደም ተሞልተዋል ታጠቡ ሰውነታችሁንም አንጹ የሥራችሁን ክፋት ከዓይኔ ፊት አስወግዱ ክፉ ማድረግን ተዉ  መልካም መሥራትን ተማሩ፥ ፍርድን ፈልጉ፥ የተገፋውን አድኑ፥ ለድሀ አደጉ ፍረዱለት ስለ መበለቲቱም ተምዋገቱ  ኑና እንዋቀስ ይላል እግዚአብሔር ኃጢአታችሁ እንደ አለላ ብትሆን እንደ አመዳይ ትነጻለች እንደ ደምም ብትቀላ እንደ ባዘቶ ትጠራለች  እሺ ብትሉ ለእኔም ብትታዘዙ፥ የምድርን በረከት ትበላላችሁ እምቢ ብትሉ ግን ብታምፁም፥ ሰይፍ ይበላችኋል የእግዚአብሔር አፍ ይህን ተናግሮአልና ፍርድ ሞልቶባት የነበረው የታመነችይቱ ከተማ እንዴት ጋለሞታ ሆነች፦ ጽድቅ አድሮባት ነበር፥ አሁን ግን ገዳዮች አሉባት ብርሽ ወደ ዝገት ተለወጠ የወይን ጠጅሽ ከውሃ ጋር ተደባለቀ ስለዚህ የእስራኤል ኃያል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ በጠላቶቼ ላይ ቍጣዬን እፈጽማለሁ፥ የሚቋቋሙኝንም እበቀላለሁ አለቆችሽ አመጸኞችና የሌቦች ባልንጀሮች ሆኑ ሁሉ ጉቦ ይወድዳሉ፥ ዋጋም ለማግኘት ይሮጣሉ ለድሀ አደጉ አይፈርዱም፥ የመበለቲቱም ሙግት ወደ እነርሱ አይደርስም እጄንም በአንቺ ላይ አመጣለሁ፥ ዝገትሽንም በጣም አነጻለሁ፥ ቆርቆሮሽንም ሁሉ አወጣለሁ ፈራጆችሽንም እንደ ቀድሞ አማካሪዎችሽንም እንደ መጀመሪያው ጊዜ መልሼ አስነሣለሁ ከዚያም በኋላ የጽድቅ ከተማ የታመነችም ከተማ ተብለሽ ትጠሪያለሽ ጽዮን በፍርድ ከእርሷም የሚመለሱ በጽድቅ ይድናሉ በደለኞችና ኃጢአተኞች ግን በአንድነት ይሰበራሉ፥ እግዚአብሔርንም የሚተዉ ይጠፋሉ በማለት ይናገራል ትንቢተ ኢሳይያስ 1 11 _ 28 መስዋዕት ማለት በሐዲስ ኪዳን አገልግሎት ትምህርት ስብከት ዝማሬ ለስሙ የሚመሰክሩ ከንፈርች እና የመሳሰሉት ቢሆኑም የእግዚአብሔር ጉዳይ ግን የመስዋዕታችን ማለት የስብከታችንና የዝማሬያችንንና የመሳሰሉትን ብዛት አይደለም እርሱ የሚፈልገው እንደባዘቶና እንደ አለላ ጠርቶና ነጽቶ የሚታየውን ሕይወታችንን ነው  ይህ ሕይወት ደግሞ መልካምን መሥራትን የሚያውቅ ፍርድን የሚፈልግ የተገፋውን የሚያድን ለደሃ አደጉ የሚፈርድ ለመበለቲቱ የሚሟገት ነው በጣም የሚገርመውና ኢሳይያስም አበክሮ የገለጸው ፍርድ ሞልቶባት የነበረው የታመነችይቱ ከተማ እንዴት ጋለሞታ ሆነች፦ ጽድቅ አድሮባት ነበር፥ አሁን ግን ገዳዮች አሉባት የሚለውን ሃሳብ ይበልጥ በጉልህ ሊያሳየን ወዶ ነው ጽድቅ አድሮባት የነበር የታመነች ከተማ አሁን ግን ጋለሞታ ሆነች ገዳዮች አሉባት መባሉ በጣም ልብን የሚነካና እጅግ የሚያሳዝንም ነገር ነው ዛሬ ላይ ያለችም የሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን ባለቤቷና የሞተላት ኢየሱስ ሲፈትሻት በአብዛኛው እንዲሁ ናት ጋለሞታ ነች ገዳዮችም አሉባት ወንድሙን የሚጠላ ሁሉ ነፍሰ ገዳይ ነውና ነፍሰ ገዳይም ሁሉ የዘላለም ሕይወት በእርሱ እንዳይኖር የታወቀ ስለሆነ  1 ዮሐንስ 3 14 እና 15 ጌታ እግዚአብሔር ወንድምን እህትን ከመጥላት በአገልግሎት ሰበብ ከመጠላላት እየተጠላሉም ከማገልገል ያድነን ከጽድቅና ከመታመን ከተማም ያወጣንን ግልሙትናችንንም እግዚአብሔር ይፈውስልን መጸሐፍ ቅዱስ የሚለን እንግዲህ መባህን በመሠዊያው ላይ ብታቀርብ፥ በዚያም ወንድምህ አንዳች በአንተ ላይ እንዳለው ብታስብ   በዚያ በመሠዊያው ፊት መባህን ትተህ ሂድ፥ አስቀድመህም ከወንድምህ ጋር ታረቅ፥ በኋላም መጥተህ መባህን አቅርብ አብረኸው በመንገድ ሳለህ ከባላጋራህ ጋር ፈጥነህ ተስማማ፤ ባላጋራ ለዳኛ እንዳይሰጥህ ዳኛም ለሎሌው፥ ወደ ወህኒም ትጣላለህ እውነት እልሃለሁ፥ የመጨረሻዋን ሳንቲም እስክትከፍል ድረስ ከቶ ከዚያ አትወጣም ይለናል የማቴዎስ ወንጌል 5 23 _ 26 ከወንድሞችና ከእህቶች ጋር ሳንታረቅ መሰውያ ላይ ቆመን የምንሰጠውን አገልግሎት እግዚአብሔር አያውቀውም ላባችን እስኪፈስ ብንናገር ብንጮህ ብንሰብክ ብንዘምርም ተቀባይነት የሌለው ስለሆነ  ዋጋ የለውም ስለዚህ መባ ከማቅረብ በፊት መታረቅ ለሕይወታችን አማራጭ የሌለውና ወሳኝ ነገር ነው መጽሐፍቅዱሳችን እንደውም የሚለው ታረቁ ብቻ ሳይሆን እርስ በርሳችሁ በኃጢአታችሁ ተናዘዙ ትፈወሱም ዘንድ እያንዳንዱ ስለ ሌላው ይጸልይ፤ የጻድቅ ሰው ጸሎት በሥራዋ እጅግ ኃይል ታደርጋለች ነው የሚለን ያዕቆብ 5 16 ስለዚህ ስንታርቅ በኃጢአታችን ተናዘን ሊሆን ይገባል ይህ ሲሆን እውነተኛ ፈውስ በወገኖች መካከል ይሆናል ይህ ሁሉ እንዲሆን ግን የእግዚአብሔር ቅዱሳን አገልጋዮች በሙሉ በአዕምሮ ወደ መታደስ መለውጥ ልንሻገር የግድ ነው ሮሜ 12 2 በዚ ጉዳይ ላይ ኢሳይያስ ብርሽ ወደ ዝገት ተለወጠ የወይን ጠጅሽ ከውሃ ጋር ተደባለቀ በማለት አለቆችሽ አመጸኞችና የሌቦች ባልንጀሮች ሆኑ ሁሉ ጉቦ ይወድዳሉ፥ ዋጋም ለማግኘት ይሮጣሉ ለድሀ አደጉ አይፈርዱም፥ የመበለቲቱም ሙግት ወደ እነርሱ አይደርስም እጄንም በአንቺ ላይ አመጣለሁ፥ ዝገትሽንም በጣም አነጻለሁ፥ ቆርቆሮሽንም ሁሉ አወጣለሁ ፈራጆችሽንም እንደ ቀድሞ አማካሪዎችሽንም እንደ መጀመሪያው ጊዜ መልሼ አስነሣለሁ ከዚያም በኋላ የጽድቅ ከተማ የታመነችም ከተማ ተብለሽ ትጠሪያለሽ ጽዮን በፍርድ ከእርሷም የሚመለሱ በጽድቅ ይድናሉ በደለኞችና ኃጢአተኞች ግን በአንድነት ይሰበራሉ፥ እግዚአብሔርንም የሚተዉ ይጠፋሉ በማለት ይናገራል ቅዱሳን ወገኖችና አገልጋዮችም በየጊዜው ባለ ሕይወታችን የታደሰ ሕይወት ስናጣ ጌታን ተቀብለን እየተለወጥን ባለንበት ወራት እንደ ብር የሚያብለጨልጨው ሕይወታችን በጊዜ ብዛት ጌታን ከመለማመድና ከከንቱ ምልልሳችን የተነሳ ሕይወታችን እንደ እስራኤል ወደ ዝገት ይለወጣል ከዚያ በኋላ እኛም እንደ እስራኤል ፈራጆች እና አለቆች አመጸኞችና የሌቦች ባልንጀሮች ለመሆን ጉቦን ለመውደድ መሮጥ በፍርድም የመበለቶችን ሙግት ቸል ማለትና አለመቀበል  የመሳሰሉትን ነገሮች ሁሉ ለማድረግ አንቸገርም ማለት እያደረግን እንገኛለን ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር አሁንም እስራኤልን እንዳላት የእኛንም ሕይወት ለመለወጥ የዛገው ሕይወታችንን ለሰዎች እያስቸገረና እየተንቋቋ ያለውን የሕይወት ቆርቆሮአችንንም ከእኛ ያወጣል ልናበራና ላንሰወር በተራራ ላይ ያለች የታመነች የጽድቅ ከተማ የምንሆነው ያኔ ነው በፊልጵስዩስ መጽሐፍ ላይ የተጻፈው ሃሳብ የሚፈጸመው በዚያን ጊዜ ነው ማለት በአሕዛብ መካከል የሕይወትን ቃል ማቅረብ ብቻ ሳይሆን ዝገታችን የነጻም በመሆኑ ያለነቀፋም የሆንን የዋሆች ነውር የሌለብን የእግዚአብሔር ልጆች የማናንጎራጉር ክፉም የማናስብ ሁሉንም የምናደርግ እንሆናለን ስለዚህ  ለእኛ ባይመስለንና በክፋታችን እየባስን ብንሄድም በአእምሮ መታደስ መለወጣችን ግን የማይቀር ነው የጠራን እግዚአብሔር ይለውጠናል


እግዚአብሔርም ደግሞ ከይሁዳ ጋር ክርክር አለው፥ ያዕቆብንም እንደ መንገዱ ይቀጣል እንደ ሥራውም ይመልስለታል
በማኅፀን ውስጥ ወንድሙን በተረከዙ ያዘው፥ በጕልማስነቱም ጊዜ ከአምላክ ጋር ታገለ
ከመልአኩም ጋር ታግሎ አሸነፈ አልቅሶም ለመነው። በቤቴልም አገኘው፥ በዚያም ከእኛ ጋር ተነጋገረ
እርሱም የሠራዊት አምላክ እግዚአብሔር ነው የመታሰቢያው ስም እግዚአብሔር ነው
ስለዚህ ወደ አምላክህ ተመለስ ምሕረትንና ፍርድን ጠብቅ፥ ዘወትርም በአምላክህ ታመን

           ትንቢተ ሆሴዕ 12 3 _ 7


እግዚአብሔር በምናነበው ቃል ይገናኘን አሜን




ቀሲስ አባ ዮናስ ጌታነህ

No comments:

Post a Comment